የትምህርት ዘርፉ እየተደረገ ላለው ሀገራዊ ዘመቻ ውጤታማነት የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከተላለፉት ውሳኔዎች መካከል ሁሉም የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለአንድ ሳምንት ዝግ እንዲሆኑ የሚለው ይገኝበታል፡፡፡፡

ውሳኔው የተላለፈው የትምህርት ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮ ከክልሎች እና ከተማ መስተዳድሮች የትምህርት ቢሮ ሃላፊዎች ጋር ባደረጉት የ ጋራ ውይይት ነው፡፡

በዚህም ትምህርት ቤቶቹ ከህዳር 27 እስከ ታህሳስ 3 ቀን 2014ዓ.ም እንደሚዘጉና ተማሪዎች፣ መምህራን እና ሰራተኞች ለዚህ ሃገራዊ ትግል እነደየአካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ አስተዋጽዖ እንዲያደርጉ ውሳኔው ያመላክታል፡፡

ትምህርት ቤቶቹ ዝግ በሚሆኑበት ወቅትም ያልተሰበሰቡ የዘማች ሰብል መሰብሰብና ቤተሰብን የመርዳት ዘመቻዎች በስፋት እደሚካሄዱ ተገልጿል፡፡

በዚህ ሂደት ትምህርት የቆመባቸው ቀናቶች በሙሉ ት/ቤቶች በሚያወጡት የማካካሻ መርሃግብር መሰረት እንዲካካስ እንደሚደረግም ተገልጿል፡፡

የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋ በመግለጫቸው ሀገር ከሌለች መኖር ስለማይቻል ሁሉም ሀገሩን የመጠበቅ ሃላፊነት አለበት ስለዚህም የትምህርት ሴክተሩ ያለበትን ሀገራዊ ሀላፊነት ይወጣል ብለዋል።

ከዚህ ባሻገር በትምህርት ዘርፉ ውስጥ ያሉ አካላት ገንዘብ በማዋጣት፣ ደም በመለገስ፣ ስንቅ በማዘጋጀት እንዲሳተፉም ውሳኔ ተላልፏል።

ተማሪዎችም በዚህ ወቅት ሀገራዊ ግዴታቸውን በመወጣት ሃገራችንን ለመገንባት በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ እንዲሳተፉም ጥሪ ቀርቧል፡፡