የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ አመራሮች፣ መምህራን፣ ሠራተኞች እና ተማሪዎች ጋር በትምህርት ጥራት ዙሪያ ምክክር አድርገዋል።

ሀገራችን አሁን ያለችበት የእርስ በእርስ ጦርነት የትምህርት ጥራትና የሞራል ውድቀት የፈጠረው ችግር ነው ያሉት የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፊሰር ብርሃኑ ነጋ ችግሩን ለመፍታት የትምህርት ጥራት ላይ ሊሰራ ይገባል ብለዋል፡፡

በሁሉም መስክ አዳዲስ ቴክኖሎጂና የፈጠራ ስራዎችን በመስራት እንደ ትውልድ መከፈል ያለበትን መስዋዕትነት ከፍለን ሃገራችንን ከድህነት ማውጣት አለብን ያሉት ሚኒስትሩ የምንሰራው የመማር ማስተማር ፣ የምርምር እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎች በእውቀት ላይ የተመሰረቱ መሆን አለባቸው ብለዋል፡፡

የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በቀጣይ የመምህራንና ሰራተኞች ብቃት ለማሳደግ፣ ትምህርትን ከፖለቲካ መለየት እና ዩኒቨርስቲዎችን ከአካባቢያዊነት ችግር ለማላቀቅ በትኩረት ይሰራል ተብሏል።

ተሳታፊዎች በበኩላቸው የትምህርትን ጥራት ለማሻሻል የምርምር ጥራት ችግርች መፈታት አሉባቸው ያላቸውን ጥያቄዎች አቅርበው ውይይት አካሂደዋል፡፡

በፕሮግራሙ ማጠቃለያ የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ፣ ሚኒስትር ዴኤታው ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌን ጨምሮ ሌሎች የትምህርት ሚኒስትር አመራሮች የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ቤተ ሙከራዎችን ጎብኝተዋል ፡፡